Sunday 5 May 2013

የሃበሻ ትዝብት


ይህ ፅሁፍ በፌስቡክ ላይ በ ItIs Mee · Sunday, 26 August 2012  የተፃፈ ነው
 
የአቶ መለስ በሞት መለየት እውነትም አስተዛዛቢና አስፈሪ እየሆነ ይመስለኛል::
በፌስ ቡክ ከሚለጠፉ እንዲሁም ከሚሰጡ አስተያየቶች በርካታ ነገሮችን መታዘብ ያስችላል:: ከፌስ ቡክ በተጨማሪ ፓልቶክ ላይ ጎራ ያለም ሰው በዚህ ሰሞን ሙሉ ለሙሉ በሚባል ሁኔታ ውይይቱ; ትችቱ; ሙገሳና ስድቡ ሁሉ አቶ መለስን ያስታከከ ነው:: ታዝቤ ዝም ማለቱ ስለከበደኝ እንዲህ ማለት ፈለኩ:: (ነገር ግን የኔ አመለካከት የርሶ ይሁን አላልኩም:: ሃሳብዎንና አመለካክከትዎን መሰንዘር ይችላሉ ነገር ግን የርሶን አመለካከት እኔ እንድጋራ እንዲገፋፉኝ አልፈልግም:: የኔም ሃሳብ እርሶን የሚገፋ አይደለም:: ከይቅርታ ጋር::)
 
ትዝብት 1. ከአቶ መለስ ምን ተማርን?

በእኔ እይታ አቶ መለስ በርካታ ነገሮችን ልንማርባቸው የሚችሉ ሰው ነበሩ:: የትምህርቱ ይዘት ግን የሚወሰነው እንደ ተማሪው አቀባበል; እይታና ፍላጎት ላይ የተመሰረተ ነው:: ሆኖም ግን ለጊዜው የተረዳሁትን በሁለት መልኩ ከፍዬ ላቅርበው:-
ሀ) ፅናት
ይህ ጉዳይ በደጋፈዎች ተቀባይነት አለው:: ነገር ግን ተቃዋሚዎች እያወቁትም ቢሆን አይዋጥላቸውም:: ለኔ ግን አቶ መለስ የአላማ ፅናትን ልንማርባቸው የሚገቡ ሰው ነበሩ:: ምክንያቴን እንዲህ ላቅርብ:- ተማሪ በነበሩበት ወቅት የነበራቸው የትምህርት አቀባበል ጎበዝ ከሚባሉት ተማሪዎች ተርታ ነበር:: እናም የህክምና ትምህርት አግኝተው ጀመሩት:: በዚያን ወቅት ድግሞ በዚህ የት/ት ዘርፍ መመረቅ ማለት የምድር ገነትን መውረስ ነበር:: ከት/ት በኋላ የሚጠብቃቸውን ህይወት ጠንቅቀው ያውቁታል:: ሆኖም ግን ውስጣቸው የነበረው ማንነትና አላማ ከዚያ አማላይ ህይወት ነጠላቸው:: እናም የህክምና ት/ታቸውን ትተው ምንም ነገር ወደሌለበት በረሃ ገቡ:: ይህ በጣም ከባድ ውሳኔ ነው:: ከባድ መሆኑን ለማሳየት ደግሞ የምናውቃቸውን ፓለቲከኞች እንዲሁም እኛን ራሳችንን መመልከት በቂ ማስረጃ ነው:: ዛሬ ፌስ ቡክ ወይም ፓልቶክ ላይ አስተያየት የሚሰጡ ሰዎች ከአላማ ይልቅ የግል ምቾታቸውን አስቀድመው ወደ አውሮፓ ወይም አሜሪካ የተጓዙ ናቸው:: እዚህ ላይ የማልከራከረው አላማቸው ትግራይን ነፃ ማውጣት እንጂ ኢትዮጵያን አልነበረም በሚለው አልከራከርም:: የፅሁፌም አላማ እርሱ አይደለም:: እናም አቶ መለስ በወጣትነት የያዙትን አላማ ለማሳካት ምንም ሳያማልላቸው መስዋዕት ሆኑለት:: መማር ለሚችል ነፍስያችን የምትጠይቀንን ጥያቄ ለመመለስ የአላማ ፅናትን ልንማርባቸው እንችላለን:: ስንቶች አላማቸው ሌላ ሆኖ ምቾት አሸንፏቸው ምቾትን መርጠው አላማቸውን ገደል ጨምረውት አይተናል::
ለ) ድፍረት
በ19 አመታቸው የትጥቅ ትግል ውስጥ መግባት ማለት በመጠኑ ከባድ ነው:: እንደርሳቸው ያሉ ቢኖሩም ለሌሎቻችን ግን 40 ወይም 50 አመት ኖሮን እንኳ ለአላማችን መሳካት ድፍረት ላጠረን መማሪያ ናቸው:: ስንቶች ፓለቲከኛ ሆነው ጀምረው ሞትን ፈርተው የሸሹ ባሉባት ሃገር እንዲህ አይነት ደፋርን ማየቱ ድፍረቱን በቀና መልኩ መማር የሚቻልም ይምሰለኛል:: ብዙው ስለሚታወቅ መዘርዘሩ አይጠቅምም:: ካሁኑ ትውልድ ደግሞ ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝን የድፍረት መማሪያ ማድረግ የሚቻልም ይመስለኛል:: ጓደኞቹ ሞትን ወይም ዱላ ወይም እስር ፈርተው ሲሸሹ አላማዬ እስከሞት ድረስ ያስደፍረኛል ያለ ወጣት ነው:: የአቶ መለስ ድፍረት አላማ ምንም ሆነ ምን ግን ማድርገ የሚችሉትንና የሚፈልጉትን አድርገው አለፉ:: እየፈለግን ድፍረቱን ላጣን መማር ያስችላል:: (ዝርዝር ነገሮችን ሁሉም ስለሚያዉቀው አለፍኩት)
ሐ) አምባ ገነንነት
ተወደደም ተጠላ አቶ መለስ አምባገነን ነበሩ:: አምባ ገነንነታቸው ደግሞ የመጣው በውስጣቸው የተፈጠረው የአላማ ቁርጠኝነት ያመጣው ነው:: እናም መማር የፈለገ አምባ ገነንነትንም መማር ይችላል:: ነገር ግን በኔ መለኪያ ከኛ አንጻር ሲታዩ አቶ መለስ አምባ ገነን አልነበሩም:: ምክንያት:- የፌስ ቡክ ወይም ፓልቶክ አስተያየት ሰጪዎች ወይም ጦማሪዎች እነሱ ብቻ ትክክል; እነሱ ብቻ አዋቂ እንዲሁም እነሱን የተቃወመ ወይም ሌላ አማራጭ ሃሳብ ይዞ አስተያየት ወይም መልስ ሲሰጣቸው ወዲያው ሪሙቭ ወይም ብሎክ በማድረግ ወይም በመሳደብ መልስ የሚሰጡ አሉ:: ነገር ግን እነዚህ ሰዎች ድሃ እያልን የምንጠራት ሃገራችን ያላትን ሃብት አውጥታ አስተምራቸው የግል ምቾት አሸንፏቸው ለባእድ እያገለገሉ ያሉ ናቸው:: እነዚህ አስተያየት ሰጭዎች በአላማቸው የመጣን ቢያገኙት ምን አይነት እርምጃ እንደሚወስዱበት መገመት ቀላል ነው:: በሃሳብ የተቃወመን መሳደብና መዛት አምባገነንነት ያልሆነ ምን ሊሆን ይችላል? ምንም ቢያጠፉም የአቶ መለስ አምባገነንነት የተሻለ ነው:: (እዚህ ላይ:- ዲያስፕኦራዎቹ የሚሰጡት አስተያየት ሰዎቹን መንግስት አባረራቸው ወዘተ ነው:: ነገር ግን ይህ ከ10 አንድ ሰው ቢሆን ነው:: ባብዛኛው የተሻለ ክፍያ ፍለጋ ወገኑን ለድንቁርናና ለበሽታ አሳልፎ ሰጥቶ የተሰደደ ጥቅመኛ ነው በኔ መመዘኛ:: ለትምህርት ተልከው ኑሮ አማሏቸው የባእድ አገልጋይ የሆኑ ብዙ እንዳሉ አንርሳ:: ሃገሩን የሚወድ ሞትንም ቢሆን መጋፈጥ አለበት በኔ እይታ::)
መ) ተጨማሪ ትምህርቶችንም መማር ይቻላል:: ነገር ግን ትምህርቶቹ ለመልካም ከተጠቀምንባቸው መልካም ይሆናሉ እንዲሁም ለክፋት ከተጠቀምንባቸው ክፉ ናቸው:: የተማሪው ምርጫ ነው ውጤቱ::

ትዝብት 2. ምን እያልን ነው?

ሀ) ደጋፊዎች
ደጋፊዎች ስለ አቶ መለስ ሲያወሩ ባብዛኛው የሚመርጡት መንገድ ግንባታ ወይም ድልድይ ወይም ግድብ ምናምን ነው:: ሆኖም በኔ መመዘኛ እነዚህ ነገሮች የመንግስት መደበኛ ስራዎች ናቸው:: በምንም መልኩ ካለፉት መንግስታት ጋር በማመዛዘን ማቅረብ የለብንም:: ዘመናቱ የተለያዩ ናቸውና:: እናም አስተማሪ የሚያስተምረው ወዶ የገባበት ስራው ስለሆነ ነው:: ነጋዴም የሚነግደው ወዶ የገባበት ስራው ስለሆነ ነው:: መንግስትም እንደዛው:: መለኪያችን መሆን ያለበት አሰራሩ ምን ያህል ፍትሃዊነት አለው? ጥራቱስ? አስተዳደሩ ምን አይነት ይዘት አለው? የሚሉ ቢሆኑ ለወደፊቱ እንዲታረሙ ይረዳሉ:: እናም ደጋፊዎች ሆይ ከላይ ያልኳቸውን ብቻ ሳይሆን አሰራሩንም በአመዛዛኝ አእምሮ መዝነን አስተያየት ብንሰጥ ፍትሃዊ ይሆናል:: ከዚህ በተጨማሪ ከአዲሱ ጠ/ሚ ጋር በተያያዘ የሚሰጡ ወይም የሚነገሩ አስተያየቶች እጅግ ያስተዛዝባሉ:: ይዘገንናሉም:: እኔ በበኩሌ አቶ መለስ ምኑን ችለው ነው የኖሩት እንድል አድርጎኛል:: የአዲሱ ጠ/ሚ ሹመት ለደጋፊዎች አልተዋጠላቸውም:: መመዘኛቸው ውስጥ የተቀመጠ መርዝ ሊኖር ይችላል ነገር ግን በደፈናው የሚሰጠው ትችት መልክ; ቆዳ; አይን; ዘር ወዘተ ነው:: እንዴት ነው ነገሩ? ኢትዮጵያችን እኮ በርካታ አካል ጉዳተኛ ሆነው ነገር ግን ልበ ብርሃን የሆኑ ሊቆች የተፈጠሩባት ሃገር ናት:: ስንቶችስ መልከ ቀና ሆነው ስራቸው የህጻናት የሆኑስ አላየን ይሆን? ቆዳ ታይቶስ እርሱ ሞኝ ነው እርሱ ብልጥ ነው ማለትን ከየት ተማርነው? ፕሮፋይላቸውን ስጎረጉር አይቼ ደግሞ የዚህ ሃሳብ አንሸራሻሪዎች ከወደ ለንደን እና ጀርመን መሆናቸውን ተረዳሁ:: እናም እንዴት ነው እንግሊዝና ጀርመን በቆዳ ይዘት ላይ የተመሰረተ ጥንቆላ ማስተማር ጀመሩ ወይ አስብሎኛል:: እባካችሁ ጭፍን ደጋፊዎች ሆይ ሃገርን መውደድ ማለት እኔ ያልኩት ብቻ ትክክል ወይም የኔ ወገን የሚሰራው ብቻ ነው ትክክል ማለት አይደለም:: አይጠቅመንም:: ሃገርን መውደድ ማለት ማንም ይሁን ማንም ብቃት ካለው አብሬው እሰራለሁ ማለት ነው:: ሃገርን መውደድ ማለት ወገንን ነጥሎ ማብጠልጠል አይደለም:: ሃገሩን የሚወድ በፈለገው መልኩ መስራትና ለውጥ ማምጣት የሚችል መሆን ያለበት ይመስለኛል:: ጥላቻን አናራግብ:: እኔ ያላከበርኩት ሰው እንዴት ሊያከብረኝ ይችላል? እኔ ያልወደድኩት እንዴት እንዲወደኝ እጠብቃለሁ? መንግስት ብቻ ነው እንዴ እኩልነትን እንዲያራምድ የምንፈልገው? እኛስ?

ለ) ተቃዋሚዎች
በተቃዋሚ ጎራ ያሉትም እንደ ደጋፊዎቹ ናቸው:: አቶ መለስ የድሮ አላማቸው ከትግራይ ጋር የተያያዘ ነበር:: አያጨቃጭቅም:: ሆኖም ግን የተፈጠረው አጋጣሚ አላማቸውን ወደ ኢትዮጵያ አሳደገው:: ይህ ደግሞ በኛ ታሪክ የነበረ ነው:: ሁሉም ነገስታት የነበራቸው ግዛት አነስተኛ ነበር:: ነገር ግን በግዜ ሂደት የሃገር ንጉስ ነው የሆኑት:: በአንድ ግዜ ሃገር የመሩት በተወሰነ መልኩ አጼ ሃ/ስላሴና ኮ/ል መንግስቱ ናቸው:: ሌሎቹ ግዛት አስፋፉ እንጅ ባንዴ የሃገር መሪ አልሆኑም:: እናም ተቃዋሚዎች እንደሚሉት አቶ መለስን ካንድ ጎሳ ጋር ብቻ አያይዞ መወንጀሉም ሆነ መውቀሱ ቢቀር ይበጃል:: መወቀስ ካለባቸው እንደ ግለስብ ሊወቀሱ ይገባቸዋል:: ከተሞገሱም እንደ ግለሰብ ሊሞገሱ ይገባል:: ተወደደም ተጠላ 21 አመት የኢትዮጵያ መሪ ነበሩ እንጅ የትግራይ መሪ አልነበሩም:: የአዲሱን ጠ/ሚ የወደፊት ብቃትም ሳይታይ ግማሹ አሻንጉሊት ናቸው ሲል ግማሹ ድግሞ እነ እከሌ አይቀበሉም ወይም ሌሎች አስተያየቶች ሲሰጡም ይታያል:: ባላየነው ነገር ላይ እርግጠኛ ባንሆን ነገር ግን ለመማማር ከሆነ ሌሎችን በማይንቅ መልኩ ቢቀርብ የተሻለ ይሆናል::
በአጠቃላይ ሲታይ ሃበሾች የምንሳሳላትን ሃገራችንን በራሳችን ግዜ ለማፍረስ እየተፍጨረጨርን እንዳለን ነው የሚታየኝ:: ሳንከባበር; ሳንፋቀር እንዲሁም ይቅር ሳንባባል እንዴት ነው አንዲት ሃገር ትኑረን የምንለው? በደባል ለመኖር የሚመኝ ያለ ካለ የሚሳካ አይመስለኝም:: ደጋፊዎችም ተቃዋሚዎችም እራሳችሁን ብትመረምሩ የተሻለ ነው:: የወደደ ቢያለቅስ ወይም የጠላ ቢስቅ ለራሱ ነው:: የፈለገንን ያህል ብናለቅስ አቶ መለስን መመለስ የምንችል አይመስለኝም:: የፈለገውን ያህል ብንጠላቸውም አቶ መለስ ተነስተው እንደገና የሚሞቱ አይመስለኝም:: በአንጻሩ ጓደኞቻችንን ማስቀየምና ጥላቻን በውስጣችን ማንገስ ነው ትርፉ:: የሰሩትን ጥፋት ለመማሪያነት ያለ ጥርጥር በቀጣይ አመታት ውስጥ እንደምናነብ እርግጠኛ ነኝ:: የሰሩትንም ጥሩ ስራ እኛ ብንክደውም አሁንም በቀጣይ አመታት ውስጥ እንድንማርበት ማንበባችን አይቀርም:: ሁሉም ጎናቸው በታሪክ ጸሃፊዎች መጻፉ ላይቀር ከጓደኞቻችን ጋር ባንቃቃር መልካም ነው ባይ ነኝ::

ትዝብት 3. የለቅሶ ባህል
አንዳንዶች የአቶ መለስ ለቅሶ ተአምር የሆነባቸው ይመስለኛል:: የናንተን ባላውቅም በኔ ማህበረስብ ውስጥ አንድ ሰው ሲሞት ለአስከሬኑ ክብር መስጠት አንዱ ባህል ነው:: አስከሬን ወደ ቤተ ክርስቲያን ወይም ወደ ሙስሊም የመቃብር ቦታ ሲሄድ ሟቹን ባናውቀውም ቆሞ እጅን ወደ ኋላ አድርጎ መሸኘት የውዴታ ግዴታ ነው:: የተጣሉ ባላንጣዎች አንዱ ሲሞት ሌላኛው ለቅሶ ይደርሳል:: ነፍስ የተጠፋፉ እንኳ ቢሆኑ በሃዘኑ ቀን ከቀሪ ቤተሰቦች ጋር አስከሬኑ ሳይቀበር ይታረቃሉ:: አልታረቅም ቢል እንኳ ለቅሶውን ደርሶ ንፍሮ ሳይበላ ቡና ሳይጠጣ ወደ ቤቱ ይሄዳል እንጅ ለቅሶ አይቀርም:: እናም አንዳንዶች ለቅሶ ደራሾችን ሲወቅሱ ሳስተውል የሃበሻነት ባህል እንዴት እየተሸረሸረ ነው አስብሎኛል:: በ1997 ምርጫ አቶ መለስ ያጠፉትን ጥፋት ማንም አይክደውም:: እኛ ብንክድ እንኳ እርሳቸው ገለልተኛ አካል ይመርምረው ተመጣጣኝ ሃይል ተጠቅሜ እንደሆን ብለው ነበር:: ይህ ሂደት በወቅቱ የተወሰደውን እርምጃ እርሳቸውም እንዳመኑበት ያሳያል:: ሆኖም ግን እነዚህን ነገሮች አሁን ማውሳቱ ምንም አይጠቅምም:: ሟቾችን አሁን ማዳን የሚቻል አይመስለኝም:: ወደፊት ታሪክ በሰፊው ያትተዋል:: ሌላው እንደ ሃገር እኮ መሪ በወጉ ታሞ በወጉ ያልተቀበረባት ሃገር ናት ያለችን:: ለሁሉም አዲስ ነን:: የእድር ሰብሳቢ እንኳ ሲሞት እኮ ለየት ያለ ለቅሶ ነው የሚደረግለት:: ከሌላው የተሻለ አስተዋጽኦ ስለነበረው:: እናም በእድር ላይ ያልተቃወምነውን የተለየ ለቅሶ በሃገር መሪ ሲደረግ እንዴት አዲስ ሆነብን? እዚህ ላይ አንዳንዶች እንደሚሉት በግዳጅ ለቅሶ ውጡ እየተባሉ የሃዘን ወቅቱን የፓለቲካ ትርፍ ማጋበሻ መደረጉን አልደግፍም:: ስህተትም ነው:: የሃገር መሪ ሞቷል ስለዚህም ሃገር ታዝናለች እንጅ ቤተ መንግስት ያሉት ብቻ ወይም ቤተ ዘመድ የሆኑት ብቻ እንዲያዝኑ ከጠበቅን ይህ ባህላችን አይደለም:: ሃብታም ወይም ባላባት እንኳ ሲሞት የሚሰበሰበዉን ለቀስተኛ ያስተዋለ ሰው አሁን መደነቅና መገረም ያለበት አይመስለኝም:: ለሁላችንም ልቦና ይስጠን:: ለሁሉም ወቀሳና ሙገሳ ይደረስበታል:: እኛ ዝም ብንል የታሪክ ተመራማሪዎቹ አይተውትም:: ምንም ለማይፈይድ ጉንጭ አልፋ የፌስ ቡክ ክርክር ወይም የፓልቶክ ስድድብ የሚያከብሩንንና የምናከብራቸውን ጓደኞቻችንን ባናጣ ይጠቅሙናል:: የዘርና የጥላቻ አባዜንም አውልቀን ወደ ቢሾፍቱ ብንልከው አይሻልም? አይበጀንም:: እውነትን መቀበል እየከበደን ውሸትን እንዴት ልንጠላ እንችላለን?

No comments:

Post a Comment