Sunday 5 May 2013

የመሪዎቻችን ብዥታ


ይህ ፅሁፍ በፌስቡክ ላይ በ ItIs Mee -Wednesday, 8 August 2012 የተፃፈ ነው

ሃገራችን ያለችበትን ሁኔታ ስናስተውለው በርካታ የተዘበራረቁ ነገሮችን እናስተውላለን:: ከነዚህ ዝብርቅርቅ ሁኔታዎች ውስጥ አንዱ የአገዛዝ ስርአት ነው:: የአገዛዝ ስርአት ሲነሳ ደግሞ የመሪው ማንነት ትልቁን ቦታ ይይዛል:: በእስከዛሬው ታሪካችን ደግሞ ለመሪዎች የተለያየ አመለካከት ስንሰጥ ኖረናል እየኖርንም ነው:: ከሰሜኑ የሃገራችን ክፍል ውስጥ ካሉት ብሄሮች የተለያዩ መሪዎች ተነስተው የተለያየ ስራ ሰርተው አልፈዋል:: ከመሃሉም እንዲሁ:: ለምሳሌም ያህል ብናይ አጼ ቴዎድሮስ አጼ ዮሃንስ እና አጼ ሚኒሊክን መጥቀስ እንችላለን:: አጼ ቴዎድሮስ በዚህም ተባለ በዚያኛው መለኪያ ሲታዩ ለሃገራችን ያደረጉት አስተዋጽኦ በርካታ ነው:: ሆኖም ግን ንጉሱ በተለያዩ ብሄሮች እይታ የተለያየ ትርጉም ይሰጣቸዋል:: ገሚሱ ለሃገራቸው ታላቅ ዉለታ የዋሉ ሲል ሌላው ደግሞ ሲወቅሳቸው እንሰማለን:: አጼ ዮሃንስም ቢሆኑ ከእንደዚህ አይነቱ ፍረጃ አላመለጡም:: ገሚሱ የተዋጣላቸው መሪ እንደነበሩ ሲያወራ ሌላው ደግሞ ሃገር የሸጡ መሪ አድርጎ ያወራል:: ከሁለቱ ነገስታት በበለጠ አጼ ሚኒሊክ ታላቁን የውዝግብ ቦታ ይወስዳሉ:: አጼ ሚኒሊክ ለሃገራችን አዳዲስ ቴክኖሎጂዎችን በማስመጣትና በመጠቀም ቀዳሚውን ቦታ ይይዛሉ:: ሌላው ቀርቶ ዘመን ተሻጋሪ የሆነና የሚጠሉዋቸው እንኩዋን ሊቀይሩት የማይደፍሩትን ቤተ መንግስት መስርተው ዛሬ ድረስ "የሚኒሊክ ቤተ መንግስት" እየተባለላቸው ይኖራል:: ሆኖም ግን በወቅቱ ከነበረው የግዛት ማስፋፋት ጋር በተያያዘ የሰሩዋቸው ስህተቶች እንዲወቀሱ አድርጓቸዋል:: በተለያዩ ሰዎችም አንዴ ሲሞገሱ ወይም እጅግ በመራር ሁኔታ ሲብጠለጠሉ ይስተዋላል:: [ቤተ መንግስታቸውን በተመለከተ ምናልባትም አጼ ሚኒሊክን የሚጠሉ ቀጣይ መሪዎች የቤተ መንግስቱን ቦታ ሊቀይሩት ይችላሉ ብዬ አስባለሁ (አይሆንም ብዬ አላስብም:: እርሳቸውን እየጠሉ ስሙን ቀይረው መኖር የሚደፍሩም አይመስለኝም)::]

በአሁኑ ሰአት ያለውም ስርአትና መሪም ላይ የተለያዩ ሰዎች የተለያየ እና ተቃራኒ አስተያየቶች መወድሶች እንዲሁም ጥላቻዎች ይሰነዝራሉ:: እነዚህ ጥላቻዎች እና ሙገሳዎች የራሳቸው አላማ ይኖራቸዋል ብዬም አስባለሁ:: ባብዛኞቹ ታዲያ ከዘር ጋር የሚያያዙ ፍረጃዎች ናቸው:: እከሌ የዚህ ብሄር አባል ሆኖ ይህንን ያህል አመት ስልጣን ላይ ቆየ አሁን ደግሞ የኛ ግዜ ነው ሲባል እናያለን እንሰማለን:: ለኔ ግን ከማንም ብሄር ይምጣ ኢትዮጵያዊ ይሁን እንጅ ጥሩ ስራ እንዲሰራ ብቻ ነው የምፈልገው:: ሁሉም እንዲህ ያስባል ብዬ መጠበቅ ደግሞ አልችልም:: መሪን በተመለከተ ያለን አመለካከት ደግሞ ይቀየራል ብሎ መጠበቅም ብዙ የሚያስኬድ አይመስለኝም:: ምናልባትም ማርስ ወይም ጨረቃ ላይም ብንሄድ ኢትዮጵያውያን መከፋፈላችን የሚቀር አይመስለኝም:: ታዲያ ምን ይደረግ?

የእኔን መፍትሄ በቀልድ ልጀምር:: ለኛ ሊሆን የሚችል መሪ ለማግኘት ሃገሪቱ ያላትን አንጡራ ሃብት አውጥታ ከ80ዎቹ ብሄር ብሄረሰቦች የተውጣጣ ዝርያ ያለው አንድ መሪ ጄኔቲክ ኢንጂነሮቹ ያዳቅሉልን:: እኛም ከተለያየ ብሄር የሚመጣን ወተት አጠጥተን እናሳድገዋለን:: እናም ያንን መሪ የትኛውም ብሄር የኔ ብቻ ነው ወይም የነሱ ነው ሳይለው ሊመራን ይችላል የሁላችንም ብሄር ተዋጽኦ ስላለበት:: ሌላኛው አማራጭ ደግሞ በትውስት ወይም በኮንትራት ከአንዱ ሃገር አንድ መሪ (ቢቻል ሁሉም የካቢኔ አባላት)  ይምጡልን:: በኮንትራት ካመጣናቸው የኛ ወይም የናንተ ስለማንል ሊመሩን ይችላሉ:: ከደበረንም ኮንትራቱን ማቋረጥ መብታችን ነው:: እኛ እንደሆነ ተስማምተን መሪውን አክብረን እሱም አክብሮን መኖር የምንችል አይመስለኝም::

ወደ ቁም ነገሬ ስመለስ ደግሞ:- ህገ መንግስታችን ያለምንም ጥርጥር መሻሻል አለበት:: ከሰሞኑ ከሚሰጡት የህገ መንግስት ጉድለቶች በተጨማሪ የመሪ የስልጣን ጊዜ እና ብሄሩን በተመለከተም በትክክል መጠቀስ አለበት:: ለምሳሌ በእያንዳንዱ የምርጫ ዙር ያሸነፈው ፓርቲ የሚያቀርበው መሪ ከምርጫው በፊት ከነበረው መሪ ብሄር የተለየ ቢሆን የተሻለ ይሆናል:: ለምሳሌ አምስት አመቱን የትግርኛ ቋንቋ ተናጋሪ ከመራ በቀጣዩ ምርጫ የሚያሸንፈው ፓርቲ ማቅረብ ያለበት መሪ ከሌሎቹ ቋንቋ ተናጋሪዎች መሆን አለበት::  ብንወቃቀስም በውጤታማነት ላይ ሊሆን ይችላል:: ቢበዛም የናንተ ብሄር የነበረው በ5 አመት ያልሰራውን የኛ በ2 አመት ሰራው እያልን ልንተቻች እንችል ይሆናል:: ቢያንስም ገዛችሁን ገዛናችሁ ከመባባል ያድነን ይሆናል:: ከዚህ በተጨማሪ ኢህአዴግ እንደገባ እና ህገ መንግስቱ እንደጸደቀ ጊዜ እንደነበረው የስልጣን ክፍፍል (ከአሁኑ የተሻል ይመስለኛል) አይነት የጠ/ሚኒስትሩ የመከላከያ ሚ/ሩ የፕሬዘዳንቱ ስልጣን እንዲሁም የሌሎቹ ሊስተካከል ይገባዋል:: የስልጣን ክፍፍሉ በትክክል የብሄር ተዋጽኦን ከነሙሉ የመወሰን ስልጣን ጋር ካልተሰጠ አለመስማማታችን የሚያባራ አይመስልም:: ለምሳሌ ከታሪካዊ ምርጫችን በሗላ ሁሉም ስልጣን በአዋጅ ወደ አንድ ሰው ተጠቃለለ:: ይህ አይነቱ አካሄድ ደግሞ መሪው ምንም ያህል ጥሩ ስራ ቢሰራ ወይም ቢያጠፋ በሁሉም ዘንድ ሊወደድ ወይም ሊጠላ እንዳይችል አድርጓል:: ምንም ያህል ጥፋት ቢያጠፋ ያጠፋ ሊመስለን አይችልም:: ደስተኛ ባልሆኑት ጎራዎች የመሪው ጥሩ ነገር አይታይም በደጋፊዎቹም መጥፎው ነገር አይታይም:: ለዚህ ደግሞ ተጠያቂው መሪው እራሱ ይሆናል የስልጣን ክፍፍሉን ፍትሃዊ አላደረገዉምና:: ስለዚህም የስልጣን ክፍፍሉ የብሄር ተዋጽኦ ይጠብቅ እንደምንለው ሁሉ የመሪውም ብሄር በዙር ቢሆን በተወሰነ መልኩ ያሉብንን አለመግባባቶች ሊቀንሰው ይችላል:: እንደ እስከዛሬው በአንድ ብሄር እየተመራን የምንቆይ ከሆነ ግን ለቀጣዩም ትውልድ እኛ የምንወቃቀስበትን የታሪክ ጉድለት አውርሰናቸው እነሱም ሳይግባቡ እንደተጨቃጨቁ እንዲኖሩ ያደርጋል::

በአሁኑ ሰአት ያሉትም መሪዎቻችን (የሃገራችንን አማካይ የእድሜ ጣሪያ ታሳቢ አድርጌ) ግፋ ቢል ከአጠቃላይ እድሜያቸው ላይ ቢበዛ ሩብ ያህሉ ቢቀራቸው ነው:: እናም ማሰብ ያለባቸው ለራሳቸው ሳይሆን ለቀጣዩ ትውልድ ሊሆን ይገባዋል:: መተቻቸት መወቃቀስ በቃን ማለት አለብን:: አንዳንዶቹ "ገና ይቀጥላል" እያሉ ቢፎክሩም ወጣቶቹ ግን መወቃቀስ እና መተቻቸት በቃን መስራትና መለወጥ እንፈልጋለን፣ ያረጀ ያፈጀ ፓለቲካዊ አመለካከት በቃን ማለት አለብን:: ቅድመ አያቶቻችን በሰሩት እኛ ልንወቀስ አይገባም:: በቅድመ አያቶቻችን ላይ የተሰራዉን በደል እያሰብን እህህ እያልን መኖር የለብንም:: ያልኖርበትን አለም መኖር የለብንም:: ታሪክን እንደ ታሪክነቱ ልንይዘው እና ልንማርበት እንጅ የልዩነት ምክንያት ልናደርገው አይገባንም:: አለም በከፍተኛ ፍጥነት እየተምዘገዘገ ባለበት ክፍለ ዘመን እኛ ግን በዘር ፓለቲካ ተወጥረን ያንተ አያቶች ያንቺ አያቶች እየተባባልን መኖር ሊበቃን ይገባል:: ይህን ካላደረግን ግን በዚያን ዘመን ከኖሩት ፊደል ካልቆጠሩት ቅድመ አያቶቻችን በምን ተሻልን? እውንስ ይህ መወቃቀስና ጥላቻስ መፍትሄ ነውን? መማራችንስ ለምን ይሆን? መማራችን ዘር ለመቁጠር ከሆነስ ባንማር ይሻለናል!!! ስሟ ሲጠራ እንባ የሚያንቀን ሃገራችን በልጅ እና ልጅ ልጆቻችን ጊዜም የድህነት ምሳሌ ሆና እንድትኖር ማድረግ የለብንም:: ለራሳችን የምንጨነቀውን ያህል በኛ ራስ ወዳድነት እና አለመግባባት የተነሳ ለቀጣዩ ትውልድ የሚሸማቀቅባትን ሃገር ላለማስረከብ መጨነቅ አለብን:: እናም የመሪን ብሄር ተመርኩዛችሁ ጭፍን ጥላቻ የምታራምዱ እንዲሁም የመሪውን ብሄር ተደግፋችሁ ጭፍን ድጋፍ የምታድርጉ ሁሉ ወደ ህሊናችሁ ተመለሱ:: ጥሩውን ጥሩ መጥፎውንም መጥፎ ማለት እንልመድ:: ለኛ ሳይሆን ለቀጣዩ ትውልድ እናስብ:: 60 ወይም 70 አመት ለማንኖርባት እድሜ ጥላቻን ተሸክመን የቀጣዩን ትውልድ ተስፋ አናመንምን:: ህገ መንግስቱም አይሻሻልም ብለው ሃይማኖታዊ ዶግማ ሊያደርጉት የሚፈልጉትንም "ለኛ ያልተስማማው እና ለልዩነታችን መንስኤ የሆነው ክፍል ወይም ቃል መሻሻል አለበት" ማለት አለብን:: የኛ የጋራ መተዳደሪያ ህግ እንጅ እያለያየ የሚያጨቃጭቀን መሆን የለበትም:: ለሁሉም የኢትዮጵያችን አምላክ መፍትሄውንና ቀና አስተሳሰብን በየልቦናችን ይጻፍልን!!! ፓለቲከኞቹንም ወደ ልቦናቸው ይመልሳቸው::

No comments:

Post a Comment