Monday 10 June 2013

"መክሸፍ እንደ ፕሮፌሰር መስፍን ወልደማርያም"

ዛሬም ይህችን ፅሁፍ በInbox ያሾለካትን ፀሃፊ እያመሰገንን እናነባለን:: የሃሳብ ፍጭት ለአንባቢያን እንደሚረዳ እምነቴ ነው::

ባለፈው ሳምንት የአንድ ፀሃፊን ፅሁፍ አንብበን ነበር:: እርሳቸውም የሰጡትን መልስ አንብቤው የተሰማኝን ጥቂት ማለት ፈለኩ::  በቀዳሚው ፅሁፋቸው ላይ እንዳወሱትና እንዳነበብነው ፅሁፋቸው "ግብፅ ሃይለኛ ዱላ ይዛ እየመጣችባችሁ ነውና አርፋችሁ ተቀመጡ" የሚል የሾርኒ መልእክት ነው የሚመስለው:: በወቅቱ ፅሁፉን ሲያዘጋጁት ለእንዲህ አይነት ትርጉም እንዳይጋለጥ አድርገው መጻፍ ይችሉ ነበር:: ሆኖም ግን ይህ የርሳቸው ነጻነት እንጂ አንባቢ ሊመክራቸው የሚገባም አይመስለኝም:: በኔ እይታ ፕሮፌሰሩ ትችት የሚባል ነገር ጠላታቸው እንደሆነ ብዙ ጊዜ ለአስተያየቶች በሚሰጡት መልስ መገንዘብ ይቻላል:: ለምሳሌ ያህልም ከዚህ በፊት ዳንኤል ክብረት መጽሃፋቸውን በመተቸቱ ከአዛውንት የማይጠበቁ ቃላትን በመጠቀም ትችቱን ሳያስተባብሉ በስድብ ጨርሰዉታል:: "የዳንኤል ክብረት ክሽፈት" በሚለው ፅሁፋቸው ላይ "....አላነበበውም ካነበበውም አልገባውም...." በሚሉ ተደጋጋሚ ቃላት አድበስብሰውት አልፈዋል:: የዚያ ትችት መልስ ዋነኛው መነሾ ዳንኤል ክብረት በትችቱ በስተመጨረሻ ላይ የጻፈው "የዶ/ሩ" ምስጢር ክፉኛ እንዳንገበገባቸው በግልፅ ያስታውቃሉ:: በርግጥም በዚያ ፅሁፍ ላይ የተጠቀሰው "ዶ/ር" የዛሬው ፕ/ር መስፍን ስለመሆናቸው በንዴት የጻፉት መልስ ራሱ ምስክር መሆኑን ብዙዎቻችን ተረድተናል:: ቀጥለውም "ፍሬ አልባ ጩኸት" በሚል ለአንባቢዎች በጻፉት መልስ ላይም አንባቢ አስተያየቱን በመስጠቱ ክፉኛ እንደተበሳጩ የሚያመለክት ፅሁፍ ፅፈው አንብበናል:: አንባቢያንንም ክፉኛ ሲሳደቡ አስተዉለናል:: አንባቢን "ሎሌህ ተነካ" ወይም "ጭፍሮቹ ተንጫጩ" በሚሉ ቃላት መልስ በመስጠት መማማር አይቻልም:: መልስ መስጠት እየተቻለም ዝም የተባለው "ሚስጥራቸው በመውጣቱ ተናደው ነው" በሚል እሳቤ ዝም እንደተባለ ግልፅ ነው::  ይልቁንም እርሳቸው ያሉቱ "የማይድን ወይም የሚድን በሽታ" መሆኑንም አስተውለንበታል:: እርሳቸው እንዳሉትም እኛ አንባቢዎች "የማያዳግም መልስ" ስለተሰጠን ሳይሆን ለአንድ አዛውንት ከዚያ በላይ መጨቃጨቅ አግባብ አይደለም በሚል እሳቤ ነው:: በግብፅ ላይ ስለጻፉትም ፅሁፍ የሰጡት መልስ አሳማኝ ሳይሆን እንደቀድሞው ሁሉ በእንካ ሰላንቲያ እና በፍረጃ የተሞላ ነው:: አሁንም ይህንን ለትዝብት እንጂ የፕሮፌሰሩ የመሳደብ መብት ሁልጊዜም የተጠበቀ ነው:: ይህንን ፅሁፍ ሲያነቡም የስድብ መልስ ሊፅፉ እንደሚችሉ ግምቴ ነው:: አሁንም መብታቸው ጥቡቅ ነው:: [ለነገሩ ፕሮፌሰሩ ብዙ ግዜ ስለመብት ሲነግሩን እናነባለን:: ሆኖም ግን በብዙ ፅሁፋቸው ስለራሳቸው መብት በሚያወሩበት ፅሁፋቸው ሌላ አካል የራሱን መብት አስከብሮ የርሳቸውንም መብት እንዲያስከብርላቸው ሲማፀኑ አስተውያለሁ::]

ፕሮፌሰሩ ያልተረዱት ሌላው ዋናው ነገር:- የፍረጃቸውን መዛባት ነው:: እኔ ሳጠይቅ "መንግስትን ለመደገፍ ለምን ድብቅ ስም ያስፈልጋል ብለው አሰቡ?" ብዬ እጠይቃለሁ:: እንደ እኔ አመለካከት መንግስት ደግፈዉ የሚፅፉለትን ሰዎች ይደግፋቸው ይሆናል እንጂ አይቃወማቸውም:: ስምን ገልጾ መፃፍ የፀሃፊው ፍላጎት ብቻ ነው:: በብዕር ስም መፃፍ ዛሬ የተጀመረ ሳይሆን ድሮም የነበረ ነው:: መፍራት አይደለም:: ዛሬ እንኳን ስምን ይቅርና የተጠቀሙበትንም ኮምፒዩተር ለይቶ ማወቅ እንደሚቻል እያወቅንማ ስማችንን በመደበቅ ብቻ ተደብቀናል ብለን የምናስብ የዋሆችም አይደለንም:: ይህንን ለመረዳት ወደ መረጃና ደህንነት ቢሮ ጎራ ቢሉ እንደሚያስረዷቸው አምናለሁ:: ዋናው ቁም ነገሩ ፅሁፉ እንጂ የሰውየው ማንነት አይደለም:: ይህ ስሜት የብዙ ሰዎች አመለካከት ነው:: በሃሳብ የማይስማማን ሰው መፈረጅ እንደ ዋና መፍትሄ መቁጠር የተካኑ በርካቶች ናቸው:: አንድ ሰው የማንኛውንም ወገን አስተሳሰብ ሳይዝ የራሱን አመለካከት ብቻ የማንፀባረቅ መብት እንዳለው መረዳት አለብን:: መንግስት ለሰራው ስራ ድጋፍ መስጠት የኢህአዴግ አባል መሆን አይደለም:: [ለመሆኑ እርሳቸው በእድሜ ዘመናቸው የስንት ፓርቲ አባል እንደሆኑና ከሁሉም ጋር ተስማምተው ሳይሰሩ እድሜያቸውን እንደገፉ አስተውለውት ይሆን?] የመንግስትንም ህፀፅ መናገር ተቃዋሚ መሆን አይደለም:: እናም ፕሮፌሰሩ እርሳቸውን የተቃወመ ወይም መንግስትን የደገፈ ሁሉ "መሃይም" እንደሆነና "ይህም ሊድን የሚችል ወይም የማይችል" እንደሆነ ሊያስረዱን ይሞክራሉ:: ነገር ግን ማገናዘብ ከሌለ መማሩ በራሱ የሚያመጣው አንዳች ረብ የለም:: ለዚህ አስረጅ ይሆን ዘንድ የመሪጌታውን በቅሎ ታሪክ ማንሳቱ ተገቢ ይሆናል:: አንዱ ተማሪ ብዙ አመት ከመሪጌታው ጋር ኖረ:: ከዚያም "አባቴ ዲቁና ይገባኛል ይሰጠኝ" ሲል ይጠይቃል:: መሪጌታውም "ምንም ሳታውቅ አይሰጥህም" ሲሉት "እንዴት ይህን ያህል ዘመን አብሬዎት ኖሬ?" ሲል ሲጠይቅ "ለዚህ ለዚህማ በቅሎዬ አስራ ሁለት አመት አብራኝ ኖራ አቡነ ዘበሰማያትን እንኳ አትችልም" አሉት የሚል አስተማሪ ታሪክ አለ:: እናም ትምህርት ቤት መኖር በራሱ የሚያመጣው ለውጥ የለውም:: ዋናው ነገሮችን ማገናዘቡ ላይ ነው ቁም ነገሩ:: እንዲያ ባይሆን ኖሮማ የታሪክ አዋቂ ሆነው "መክሸፍ እንደ ኢትዮጵያ ታሪክ" ብለው ባልፃፉልን ነበር:: ለመሆኑ ታሪካችንን ማነው የፃፈልን? እነርሱ አይደሉምን? ዳንኤል ክብረት እንደጠየቀው ሁሉ "የኛ ታሪክ ሲጻፍ እርሶ የት ነበሩ"? ብዬ እጠይቃቸዋለሁ:: "ወይስ ቆይቶ አንድ ትውልድ ሲያልፍ ነው የተረዱት" ብዬ እጨምራለሁ::

 ሌላው የፕሮፌሰሩ አመላለስ ግራ አጋቢ ሆኖ ነው ያገኘሁት:: በርሳቸው እድሜና የትምህርት ደረጃ ላይ ያለ ሰው ለወጣቶች መከባበርን እና መደማመጥን እንጂ በስድብ መመላለስን ሊያስተምረን ባልተገባ ነበር:: ሆኖም ግን እርሳቸው የሚፈልጉት የራሳቸውን ዝና እንጂ ይህን አይነቱን ቅዱስ ተግባር የሚፈልጉት አይመስሉም:: ይህም መብታቸው ነው:: ነገር ግን በሚፅፉት ፅሁፍ አሳቢ በመምሰል ሊያደነቁሩን እና የርሳቸውን የተሳሳተ አመለካከት ሊያጋቡብን ሲተጉ ዝም ብሎ ማየት የሚቻል አይመስለኝም:: ይህንን የተሳሳተ መንገድ ለማስተዋል ባለፈው ሳምንት "ፕሮፌሰር መስፍን የዘመኑ አፈወርቅ ገብረየሱስ" በሚል ርዕስ የተጻፈውን ፅሁፍ ማስታወሱ ጥሩ ነው:: ጸሃፊው እንደገለፀው ፕሮፌሰሩ በተደጋጋሚ ግዜያቶች በፓርቲዎች ውስጥ አባል ሆነውም ሆነ ሳይሆኑ ሲገቡ አውቀውት ይሁን ወይም አይሁን ለመከፋፈል ሲተጉ ይስተዋላሉ:: ለዚህም የቀድሞዉን የቅንጅትን ችግሮች ማስታወስ ሲቻል ከዚያም ቀጥለው አንድነትን ለመከፋፈል ያልፈነቀሉት ድንጋይ አልነበረም:: እናም ፀሃፊው ትዝብቱን ሲያስቀምጥ እርሳቸው በበኩላቸው "አላደረኩም ወይም ያደረኩት ይህንን ነው" ማለት ሲገባቸው መልሳቸው ያልተገባ ሆነ:: በአጠቃላዩ ሲታይ ሰውየው የፖለቲካ ፓርቲዎች ተስማምተው ለሃገር ሲሰሩ ማየት የሚያማቸው ይመስሉኛል:: የዚህ ዘመን ትውልድ ደግሞ እንዲህ ያለው የመጠላለፍ ድራማ አንገፍግፎታል:: ቢቻል እና ብንታደል ሁሉም ፓርቲዎች በልዩነታቸው ተስማምተው ለሃገራችን ቢሰሩ ደስ ይለናል እንጂ አይከፋንም:: የፖለቲካ ልዩነት ሌላ ፥ የሃገር ጉዳይ ደግሞ ሌላ ነው:: ዘመን በተሻገረ የጥላቻ ፖለቲካ እንዲሁም የ"እኔ ብቻ አዋቂ" ፍልስፍና ዛሬም ድሆች ከመባል አላዳነንም:: ዛሬ መስራትና መለወጥ እንጂ የተዛባ አጼያዊ የፖለቲካ አመለካከት አንገሽግሾናል:: እናም የሚሰሙኝ ከሆነ 'ፕሮፌሰር መስፍን ሆይ ኢህአዴግን የተቃወመ ሁሉ "የተቃዋሚ ፓርቲ አባል" አይደለም:: ኢህአዴግን የደገፈ ሁሉ ደግሞ "የኢህአዴግ አባል" አይደለም' ልላቸው እወዳለሁ:: ለሃገር የሚጠቅም ሃሳብ ያለውን ሁሉ እንደግፋለን:: አፍራሽ የሆነውን ሁሉ እንቃወማለን:: መጠላለፍ በቃን:: ከተቻላቸው እነርሱው በመጠላለፍ ታሪካቸው ይቀጥሉ:: አመለካከታቸውን ወደኛ ለማስተላለፍ ጥረታቸውን ቢተውን አይሻልም ይሆን? ስድብ በማስተማርስ እኛን ከአፍራሽ አስተሳሰብ መጠበቅ ይቻል ይሆን? እርሳቸውም ከቻሉ ራሳቸውን በድጋሚ ጡረታ ቢያወጡ ደስ ይለናል:: በመጨረሻም:- ተቺዎችን በመሳደብ ብቻ ራስን አዋቂ አድርጎ ማሳየት ይቻል ይሆን? ሞጋች ሃሳብ ያቀረበ ሁሉ ለርሳቸው "መሃይም" ነው:: ለርሳቸው "ወኔ ቢስ" ነው:: የተከራከረን ሰው ሁሉ "የእገሌ ጭፍራ" በማለትና በመፈረጅ ራስን ማጉላትስ ይቻል ይሆን? ይህንን የሚያውቁት እርሳቸው ናቸው:: ከተማሪዎቻቸውስ እንደርሳቸው ስድብን የተካነ ይኖር ይሆን?
                                         ቸር ወሬ ያሰማን:: አንተነህ ነኝ::

No comments:

Post a Comment