Monday 24 June 2013

እግር ኳስ ፌዴሬሽን ከሁለት ወር በኋላ እንዲበተን ተወሰነ!!

“እንድትቆዩ ማህተም እንድንሰጣችሁ አስባችሁ ከሆነ ተሳስታችሁዋል፣ ኢትዮጵያ ቡናን ወክዬ ይህንን አላደርግም” መቶ አለቃ ፈቃደ ማሞ

“በአንደኛ ደረጃ ጥፋተኛነቴ ባይዋጥልኝም ከኔ ክብር ያገር ክብር ይበልጣል” አቶ ብርሀኑ ከበደ

“ራሳችን ላይ ሌላ ችግር አናምጣ ሁለት ወር ነገ ነው” ተሳታፊ

“ከዚሁ ልንገራችሁ እንለቃለን…. ለአዲሱ ትውልድ እናመቻቻለን”  አቶ ሳህሉ ገ/ወልድ 

“ከካፍና ከፊፋ የሚላክ የስብሰባ ደብዳቤ ትረሳለችሁ?”

images
የኢትዮጵያጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ባካሄደው አስቸኳይ ጉባኤ የፌዴሬሽኑ አመራሮች ከሁለት ወር በሁዋላ መስከረም ወር ላይ በሚካሄድ ጠቅላላ ጉባኤ ከሃላፊነታቸው እንዲነሱ ተወሰነ። በጉባኤው መጨረሻ ላይ ፕሬዙዳንቱ አቶ ሳህሉ ገ/ወልድ ” ከወዲሁ ልንገራችሁ ሁላችንም እንለቃለን፣ለአዲሱ ትውልድ እናመቻቻለን” በማለት ውሳኔውን እንደሚያከብሩ አስታውቀዋል። ስራ አስፈጻሚዎቹ የሰሩት ጥፋት ክፍተኛ በመሆኑ “ከሃላፊነታቸው ይነሱ” በሚሉና  ” ይቆዩ” በሚሉት መካከል ክርክር የተካሄደና ክርክሩም የጋለ እንደነበር ኢቲቪ ዘግቧል።

በጉባኤው ላይ አስተያየት የሰጡት የኢትዮጵያ ቡና እግር ኳስ ክለብ ፕሬዚዳንት ” ዛሬ ይህ ጠቅላላ ጉባኤ የተጠራው እናንተ እንድትቆዩ ማህተም እንዲሰጣችሁ አስባችሁ ከሆነ ተሳስታችሁዋል። እኔ ኢትዮጵያ ቡናን ወክዬ እንዲህ ያለ ፈቃድ አልሰጥም” በማለት ህዝባዊነታቸውን አረጋግጠዋል። ሌላ ተሳታፊ ጉባኤተኛ ”ከካፍና ከፊፋ የስብሰባ ደብዳቤ ፋክስ ሲደረግላችሁ ትረሱታላችሁ?” ሲሉ ለስብሰባና ለአበል የሚደረገውን ፍትጊያ በንጽጽር በማቅረብ ስራ አስፈጻሚዎቹን ወርፈዋቸዋል።
የብሔራዊ ቡድን መሪና የፌዴሬሽኑ ምክትል ፕሬዚዳንት አቶ ብርሃኑ ከበደ ”በአንደኛ ደራጃ ጥፋተኛነቴ ባይዋጥልኝም የኔ ክብር ካገር አይበልጥም” በማለት ራሳቸውን ከፌዴሬሽኑ ማግለላቸውን ተናግረዋል። እሳቸው አማተር አገልጋይ ሆነው የመጀመሪያው የጥፋተኛነት ጽዋ መቅመሳቸውን ለቤቱ ፍርድ እንደሚተውት አስታውቀዋል።

አስቀድመው አገርና ህዝብን አሁን ደግሞ ጠቅላላ ጉባኤውን ”ጥፋተኛ ነን፣ ትፋተኛነቱን ሙሉ በሙሉ እንወስዳለን” በማለት ይቅርታ የጠየቁት አቶ ሳህሉ ”ከወዲሁ ልንገራችሁ በመስከረም በሚካሄደው ጉባኤ እንለቃለን” ሲሉ ፌዴሬሽኑ ባዲስ አመራር እንደሚተካ ይፋ አድርገዋል። አቶ ብርሃኑ ያቀረቡት መልቀቂያ በ82 ድምጽ፣ በ 2 ተቃውሞና በ3 ድምጸ ተአቅቦ ውድቅ ተደርጓል።
ዶ/ር አሸብር ወ/ጊዮርጊስና  አቶ አብነት ገ/መስቀል በገጠሙት ጸብ የተነሳ ታምሶና አገር እስከማስቀጣት ደርሶ የነበረው ፌዴሬሽኑ ውዝግብ ክፍተኛ ገንዘብ ፈሶበት ”ተረጭቶ” በአቶ አብነት አሸናፊነት ከተጠናቀቀ በሁዋላ ፌዴሬሽኑን ወደፊት ያራምዱታል፣ የህዝብ አመኔታና ሙያዊ ብቃት አላቸው የሚባሉ ሰዎች እንዳይመረጡ አሁንም በገንዘብ በተሰራ ስራ ፌዴሬሽኑ ከችግር እንደማይወጣ በተደጋጋሚ ሲነገር ነበር። ይሁንና መንግስትም ባለድርሻ አካልትም መስማት ባለመቻላቸው ፌዴሬሽኑ የግለሰብ መፈንጫና ዐሽከር የሆነ ተቋም እንዲሆን ተደርጎ ነበር።

መንግስት አሁን በድጋሚ የሚደረገውን ምርጫ ጥንቃቄ ሊወስድ እንደሚገባው የሚታመነው ካለፈው  ተሞክሮ ነው። ለዚህም ይመስላል የስፖርት ኮሚሽነሩ አቶ አብዲሳ ያደታ ”ታላቅ ትምህርት እንወስድበታለን” ሲሉ የተሰሙት። ከዚህ መንፈስ ተነስተው ዳግም ስህተት አይፈጠርም ካሉ፣ ስፖርቱን ከኮታና በብሔር ተዋጽኦ ላይ እንዲንጠለጠል ማድረግ ከጥቅሙ ጉዳቱ ማመዘኑ በተደጋጋሚ የታየ በመሆኑ፣ ገንዘብ አለን የሚሉ ”ከአገር ተበድረው ለገስን በሚሉት የእዳ ብር” የሚፈጽሙት ለነሱ ” የዝና” ለህዝብና ለባለድርሳዎች ”ውርደት” የሆነ አሰራር እንዳይደገም   ከወዲሁ ጥንቃቄ መደረግ ይኖርበታል። የስፖርት ዘርፍ ጋዜጠኞችም ከይሉኝታ በዘለለ ለመስከረሙ ምርጫ አስፈላጊውን አቅጣጫ የማሳየትና ስፖርቱን ሊያሳድጉ የሚችሉ ዜጎችን በማመላከት፣ የቀድሞውን ስህተት በማሳየት ገንቢ ተግባር መጫወት አለባቸው። እነ አጅሬን አሁንም ጠንቀቅ!!

ይህ ፅሁፍ ከ Yabedew ብሎግ ላይ ነው::

No comments:

Post a Comment